Tuesday, December 9, 2014

የቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ኢትዮጵያ
ቴዎድሮስ ተ/አረጋይ
ማለዳ ፌስቡክ እንዴት አደረ? ብዬ ስከፍት የተዋናይት ሜሮን ጌትነትን ለወሊድ አሜሪካ ልትሄድ መሆኑን አንብቤ ቴዲ አፍሮ ትዝ አለኝ ። የሜሮን አይገርምም ። አሁን ልጆቻቸው ኢትዮጵያ እንዲወለዱ የሚፈቅዱ ወላጆች ጥቂት ወይም እዚያ የመውለድ እድሉ የሌላቸው ናቸው ። የባለሀብት ፣ የባለስልጣን ፣ የፓይለት ፣ የሆስቴስ ፣ ወዘተ ልጆች አሜሪካ ነው በብዛት የሚወለዱት ። ለብዙዎች ኢትዮጵያ አንደ ቀን አሜሪካ ጠቅለው እስኪሄዱ መሸጋገሪያቸው ናት ። እነዚህ ኢትዮጵያ የልጃቸው መኖሪያ እንድትሆን ያልፈቀዱ ዜጎች "ኢትዮጵያ ሀገሬ እወድሻለሁ " ሊሉ እንዴት ይችላሉ? ሰው እንዴት በእንግድነት ካለበት ቤት ፍቅር ሊወድቅ ይችላል? ምንድነው ሀገር መውደድ? አጋጣሚ ሆኖ ደግሞ እነዚህ ሀገሪቱን ጊዜያዊ መኖሪያ ያደረጉና በቀጣይ ሀገሪቱ የተሻለች መኖሪያነቷ ላይ ጥያቄ ያላቸው ዜጎች የሚበዙቱ የስርዓቱ ተጠቃሚዎች መሆናቸው ነው ።
በዚህ ስርዓት ቅጠቀጣ የበዛበት ድምፃዊ ቴዲ አፍሮ ከሀገር ለመውጣትና እዚያው ለመኖር በቂ ምክንያት አለው ። ድምፃዊው ግን ብልጥ ብቻ ሳይሆን ብልህ ነው ። ከሀገሩ ቢወጣ ከባህር የወጣ አሳ እንደሚሆን ያምናል ። ከነችግሩም ሀገርና ህዝብ እንደሚበልጡ ይረዳል ። ከሀገር ወጥተው ከባህር የወጡትን ያያል ። ከዚህ ሁሉ በላይ ሀገሩን ይወዳል ። ይህች የሚወዳት ሀገሩ ለእሱ ባትመቸው እንኳ ለልጆቹ የመኖሪያ ሀገር መሆኗ ላይ ጥያቄ አላነሳም ። ልጆቹን ለሀገሩ ነው የሰጣቸው ። ስለዚህም ባለቤቱ አምለሰት እርግዝናዋ ገፍቶም እዚያች ለብዙዎች " የተስፋዪቱ ምድር " የሆነች ሀገር ስትቆይ እዚያው እንደምትወልድ ነበር የገመቱት ። አምለሰት ግን ብዙዎች ወደዚያ በሚሄዱበት ወቅት ወደዚህ መጣች ። የቴዲ ልጅ ኢትዮጵያዊ ሆኖ ተወለደ ። ይህ ብዙ ማለት ነው ። ትልቅ ውሳኔ ነው ። በሀገር ለመማረርና ሀገርን " ለመጥላት" ፣ ቢያንስ በሀገርና በስርዓቱ (ብዙዎች ዘላቂዋን ሀገርና ነገ የሚወድቀውን ስርዓት ለይተው አያዪም) እምነት ለማጣት ቴዲ ይቀርባል ። ይህ ሁሉ ግን ልጁን አሜሪካዊ ለማድረግ ውሀ የሚቋጥር ምክንያት አልሆነለትም ። ስለዚህ የቴዲን ሀገሬ እሰማታለሁ ። ሀገሬ ሲል እውነትም ሀገሩን እያሰበ ነው ። ቴዲ " ሀገሬ ለእኔ የሙዚቃ ግጥም ማድመቂያዬ አይደለችም ፤ ሀገሬ ናት " ቢለኝ አምነዋለሁ ። ብዙዎች ግን አፋቸው እንጂ ተግባራቸው ይህን አይልም ። የቴዲ አፍሮ ኢትየጵያ በስሟ ግጥም የሚሰራላት ፣ ዜማ የሚንቆረቆርላት ፣ ብር የሚታፈስባት ብቻ አይደለችም ። እንደ ትናንቱ ሁሉ ዜግነቷ የሚወደድ በጭንቅ ውስጥ ያለች የተስፋ ሀገር ናት ። ቴዲ ልጆቹን በጉዲፈቻ ማሳደግ የፈቀደ ክፉ አባት አይደለም ። የሚዘፍንላትና በዘፈኑም ሀብት ያፈራባትን ሀገሩን የንግድ መደብር አላደረጋትም ። መኖሪያውና የልጆቹ ማደጊያ እንድትሆን መርጧታል ። ብዙዊች ግን ፣ የቴዲ ከሳሾችም ጭምር ይህ የሀገርን ሀገሬ የማለትና ባለሀገር የመሆን ሞራላዊ ድፍረት በውስጣቸው የለም ።

1 comment: